v1

የቀጥታ የቡና ግብይት ሥርዓትን በማጠናከር የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተሰራ ነው – ክቡር ግርማ አመንቴ (ዶ/ር)

የካቲት 29/2016

ኢ∕ቡ∕ሻ∕

የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን የቀጥታ የቡና ግብይት ሥርዓትን በማጠናከር የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑን የግብርና ሚኒስትሩ ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) ገለፁ።

ይህ የተገለፀው በዛሬው እለት የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለሥልጣን የቀጥታ የገበያ ትስስር ሥርዓት አስመልክቶ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በኢሊሊ ሆቴል ውይይት ባካሄደበት ወቅት ነው።

የግብርና ሚኒስትሩ ክቡር ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) በዚህ ጊዜ እንደገለፁት መንግሥት ለቡና ምርትና ምርታማነት ማደግና የግብይት ሥርዓት መቀላጠፍ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ነው። በተለይም የግብይት አማራጮችን በማስፋት አርሶ አደሩ ተጠቃሚ እንዲሆን እየተሰራ መሆኑንና የቀጥታ ትስስር ሥርዓት ትኩረት መደረጉን ነው የገለጹት።

የቡና የግብይት እሴት ሰንሰለት ውስጥ አርሶ አደሩን ተጠቃሚ የሚሆንበት ሁኔታ መፍጠር ተገቢ እንደሆነ አብራርተው ይህም ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ያግዛል ያሉት ክቡር ሚኒስትሩ ቀጥታ የገበያ ትስስር ሥርዓት አርሶ አደሩን ተጠቃሚ የሚያደርግ በመሆኑ ሥርዓቱ ያሉበትን ክፍተቶች በማረምና አዎንታዊ ጎኑን በማጠናከር የበለጠ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።

የቡናና ሻይ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ክቡር አዱኛ ደበላ (ዶ/ር) በበኩላቸው የቀጥታ የገበያ ትስስር ሥርዓት አርሶ አደሩን ከገበያ ጋር በማገናኘት ቡናውን በቀጥታ ለውጭ ገበያ ማቅረብ አስችሏል ብለዋል።

ቡና አምራች፣ አቅራቢና ላኪም ወደ ቀጥታ የገበያ ትስስር በመግባታቸው አሁን ላይ 90 በመቶ የሚሆነው የውጭ የቡና ንግድ በዚህ የግብይት አማራጭ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን የተናገሩት ዶ∕ር አዱኛ በዚህም ቡና አምራች፣ አቅራቢና ላኪ በእሴት ሰንሰለቱ የሚገባቸውን ጥቅም ከማግኘታቸው በዘለለ ጥራትና ብዛት ያለው ቡና ለዓለም ገበያ በማቅረብ ተወዳዳሪ መሆን ተችሏል ብለዋል።

አስተያየታቸውን የሰጡ የቡና አቅራቢ አርሶ አደሮች የቀጥታ የገበያ ትስስር ግብይት አምራቾችን አቅራቢውንና ላኪውን በማገናኘት ጥራት ያለው ቡና ለውጭ ገበያ እንዲቀርብ በማድረግ አገርና አርሶ አደሩን ተጠቃሚ እያደረገ ይገኛል ብለዋል።

የቀጥታ ትስስር ግብይት የሚስተዋሉ ችግሮችን በመቅረፍ የበለጠ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አስተያየት ሰጪዎቹ ተናግረዋል።

Tags: No tags

Add a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *